የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መምሪያ

ለዚህ ሳምንት ጥናት የሚከተሉትን ጥቅሶች ያንብቡ፡ ዘኍ. 13:6፣ 30-32፣ ኢያሱ 14:6-14፣ ሉቃስ 18:1-5፣ ኢያሱ 19:49-51፣ 2 ቆሮ. 3:18፣ ሮሜ፡ 12፡1-2።
የመታሰቢያ ጥቅስ፡ “እግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን
አስቡ፥ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው
ምሰሉአቸው።” (ዕብ 13፡7)
ሁሉም ወላጅ ልጆቹ ሌሎች ሲያደርጉ በማየት እንደሚማሩ
ያውቃል፣ አይደል? ልጆቻቸው ከመልካም ባህሪያቸው ይልቅ
መጥፎ ባህሪያቸውን ሲከተሉ በማየታቸው የተናደዱ ስንት
ወላጆች ናቸው? እድሜያችን ምንም ይሁን ምን መልካሙን ከማድረግ ይልቅ
ስህተት መስራት ይቀለናል። የወደቁ ፍጥረታት የመሆን አንድ ክፍል ይህ ነው።
“የምጠላውን ያን አደርጋለሁና ዳሩ ግን የምወደውን እርሱን አላደርገውም።”
(ሮሜ. 7፡15)። ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ያልሆነ ማን አለ?
ሰዎች ከተወለዱበት ጊዜ ጀምሮ የተቀረጹት በምሳሌነት ኃይል ነው።
በሕይወታችን ውስጥ በጣም መሠረታዊ የሆኑትን እንደ መራመድ፣ ማውራት
እና ስሜታችንን መግለጽ የምንማረው የቅርብ ሰዎችን በመምሰል ነው።
ጎልማሶች እንደመሆናችን አሁንም አርአያዎች እንፈልጋለን፣ ምንም እንኳን
ፍጹም ባይሆኑም፣ እነዚያን ሰዎች የእምነት ጀግና ያደረጓቸውን መንፈሳዊ
ባህሪያት ልናደንቅ እና ልንኮርጅ እንችላለን።
በዚህ ሳምንት፣ በመጽሐፈ ኢያሱ ውስጥ የሚገኙትን የሁለት ግዙፍ
የእምነት ሰዎች ምሳሌዎችን ካሌብ እና ኢያሱን በጥልቀት እንመረምራለን።
በእስራኤላውያን ታሪክ ውስጥ በጣም ወሳኝ ከሆኑት ወቅቶች በአንዱ
በትውልዳቸው ውስጥ ጎልተው እንዲወጡና በአምላክ ሕዝቦች ሕይወት
ውስጥ ቁልፍ ሚና እንዲጫወቱ ያደረጋቸው ምንድን ነው?
ለህዳር 13 ሰንበት ለመዘጋጀት የዚህን ሳምንት ትምህርት ያጥኑ።
ዘፍጥረት 36:15፣ ዘኍልቍ 13:6፣ 30-32፣ እና ኢያሱ 14:6፣ 14ን ያንብቡ።
ካሌብ ማን ነበር? በእስራኤል ሕዝብ መካከል ያለው ቦታ ምን ነበር?
የካሌብ ስም በብሉይ ኪዳን ሁልጊዜ በአሉታዊ አውድ ውስጥ ከሚገኘው ኬሌብ “ውሻ” ከሚለው የዕብራይስጥ ቃል የመጣ ነው። ነገር ግን፣ ኬሌብ የአገልጋዩን ድፍረት፣ ጽናት እና ለጌታው ያለውን ታማኝነት ለመግለጽ ከመጽሐፍ ቅዱሳዊ ውጪ በሆኑ ፊደሎች እና መዝሙሮች ውስጥ ጥቅም ላይ ውሏል። በዚህ ረገድ፣ ካሌብ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ለጌታው ያለውን ታማኝነት በማሳየት ከስሙ ጋር የሚገጥም ህይወት ኖሯል። ካሌብ አብዛኞቹ ሰላዮች ፈጽሞ የተለየ አመለካከት ቢኖራቸውም እና የእስራኤል ሰዎች እንደሚገድሉት ቢዝቱበትም ሐሳቡን ለመናገር ፈቃደኛ መሆኑ ስለ ካሌብ ምን ይነግረናል? ዘኁ. 14:6-10፣ 21-25፣ ዘሁ. 26:65፣ ዘሁ. 32፡12ን ይመልከቱ።
በኢያሱና በካሌብ ዘመን የነበሩትን እነዚህን ወሳኝ የእስራኤል መሪዎችን
ይመልከቱ፡ ሻሙአ፣ ሻፋጥ፣ ኢጋል፣ ፓልቲ፣ ጋዲኤል፣ ጋዲ፣ አሚኤል፣ ሴቱር፣
ናህቢ እና ግኡኤል። እነዚህ ስሞች ይታወቃሉ?
በአብዛኛው አይታወቁም። ለምን? ምክንያቱም እነሱ የከነዓንን ምድር
እንዲጎበኙ ሙሴ የላካቸው አሥሩ ሰላዮች ናቸው። የተረሱት ስማቸው
ሊታወስ የማይገባ በመሆኑ ነው። ያመጡት ዘገባ የተስፋይቱን ምድር መውረስ
የማይቻል አድርጎ ገልጿል። በአንዳንድ የምድሪቱ አካባቢዎች ከሚኖሩት
ግዙፎች ጋር ሲነጻጸሩ እራሳቸውን እንደ አንበጣ አድርገው ይመለከቱ ነበር፣
እና በከነዓን ባሉ የተመሸጉ ከተሞች “ጸንቶ የማይኖር” ቅጥር ፊት ልባቸው
በፍርሃት ቀለጠ።
አዎንታዊ ዘገባ ካመጡት ሁለቱ ሰላዮች መካከል ታላቅ የሆነው ካሌብ
ሌላ አማራጭ በማቅረብ ረገድ ግንባር ቀደም ሆኗል። ምንም እንኳን ሊሞት
በሚችልበት ሁኔታ ተቃውሞ ቢገጥመውም ትክክል እንደሆነ ለሚያውቀው
ነገር ለመናገር ፈቃደኛ ነበር፡- “ማኅበሩ ሁሉ ግን በድንጋይ ይወግሩአቸው
ዘንድ ተማከሩ።” (ዘኍ. 14:10)
በዙሪያችሁ ያሉ ብዙ ሰዎች በተለይም ከእናንተ ጥልቅ እምነት ጋር በሚቃረን
መልኩ የተለየ አስተያየት ያላቸው ሲመስሉ ምን ታደርጋላችሁ?
ኢያሱ 14:6-14፣ ዘኁልቁ 14:24፣ ዘኁልቁ 32:12፣ ዘዳግም 1:36 እና ሉቃስ 6:45ን ያንብቡ። የካሌብንና የኢያሱን አመለካከት እንዴት ትገልፁታላችሁ? ጌታን በሙላት መከተል ማለት ምን ማለት ነው?
ካሌብ እግሩ የረገጣትን ምድር እንደሚወርስ እግዚአብሔር በሙሴ
አማካይነት የሰጠውን ቃል ኪዳን ፈጽሞ አልረሳም (ዘኁ. 14፡24)። ከአርባ
ዓመታት በኋላ፣ ስለ ምድሪቱ “በልቤ የነበረውን” (ኢያሱ 14፡7) በማለት
የራሱን ዘገባ ይጠቅሳል ። ዘገባው የተመሠረተው በአምላክ አመራርና እርዳታ
እስራኤላውያን ምድሪቱን እንደሚቆጣጠሩ ባለው እምነት ላይ ነበር።
በእስራኤላውያን መካከል ፍርሃት እንዲፈጠር ካደረጉት ከሌሎቹ
አሥሩ ሰላዮች ዘገባ በተለየ፣ ካሌብ በይሖዋ የተስፋ ቃል ላይ በሙሉ ልብ
መታመኑን አሳየ። የዕብራይስጡ ሐረግ፣ ቀጥተኛ ትርጉሙ “እግዚአብሔርን
በሙላት እከተለው ነበር” (ኢያሱ 14፡8) የሚለው በአጭሩ የተቀመጠ ሲሆን
“ልቤ እግዚአብሔርን ሙሉ በሙሉ ተከተለው” ወይም “ከእግዚአብሔር ኋላ
ለመሄድ ልቤን ሞላሁ” የሚል ረዘም ያለ ዘይቤያዊ አነጋገር ሊሆን ይችላል።
የባዕድ አማልክትን ከተከተሉ እና ጌታን ሙሉ በሙሉ ካልተከተሉት ሰዎች
በተቃራኒ የካሌብ ልብ ሙሉ በሙሉ ለጌታ የተሰጠ ሰው ነበር።
የካሌብ ታማኝነት ላይ አጽንዖት በመስጠት ተመሳሳዩ አገላለጽ ሁለት
ጊዜ ተደግሟል (ኢያሱ 14: 9፣ 14)። ባህሪው ካሌብን ከሌሎቹ አስር ሰላዮች
ከሚለየውና ጌታ ራሱ “ልዩ መንፈስ” (ዘኁ. 14፡24) ካለው ጋር የሚገጥም ነው።
በ85 ዓመት ዕድሜው እንኳን፣ ልባቸው ለእርሱ እና ለዓላማው ሙሉ በሙሉ
የወሰኑ ሰዎች ጌታ ሊያሳካላቸው ስለሚችለው ነገር ምሳሌ ሆኖ ቀጥሏል።
ካሌብ እያንዳንዱ ነገድ በመጨረሻ የሚይዘው መሬት የጌታን የተስፋ
ቃል ለመጠየቅ ከደፈሩበት መጠን እና በእምነት ለመርገጥ ፈቃደኛ ከነበሩበት
መሬት መጠን ጋር በቀጥታ የተዛመደ እንደሆነ ተረድቷል። የአምላክ የተስፋ ቃላት
የእኛ ፈቃድ ምንም ይሁን ምን በራሳቸው የሚፈፀሙ አይደሉም። ይልቁንም
በቆራጥ እርምጃ የታጀበ እምነትን ይፈልጋሉ። ኡላይ “ምናልባት” (ኢያሱ 14:12)
የሚለው የዕብራይስጥ ቃል ፍርሃትንና ጥርጣሬን ሊገልጽ ይችላል፣ነገር ግን
አብዛኛውን ጊዜ የሚያመለክተው አዎንታዊ ነገር እንደሚፈጸም ያለን ተስፋና
ግምት ነው (ዘፍ. 16:2፣ ዘኍ. 22:6፣ 11፣ ዘኍ. 23:3)።
ጌታን ሙሉ በሙሉ ከመከተል የሚያግዱን ፣ “ትንንሽ” ማመቻመቾች ምንድን
ናቸው?
ኢያሱ 15፡16-19፣ መሳፍንት 1፡13 እና መሳፍንት 3፡7-11 ያንብቡ። ይህ ታሪክ ስለ ተምሳሌትነት ኃይል ምን ይነግረናል? የካሌብ አመለካከት በወጣቱ ትውልድ ውስጥ የተስፋፋው በምን መልኩ ነበር?
በዚህ ክፍል ውስጥ፣ ካሌብ ቂርያትሴፌርን(ዳቤርን) ለሚመታ እና
ለሚይዛት ሴት ልጁን አክሳን እንደሚያጋባው ተናገረ። ጎቶንያል ከተማይቱን
አሸንፎ ስለያዘ አክሳን ማግባት ቻለ። የካሌብን ድፍረት፣ እምነት እና ፈተናዎችን
ለመወጣት ያለውን ዝግጁነት በድጋሚ ስለሚያሳይ ይህ ታሪክ አስፈላጊ ነው ።
በተጨማሪም ቀጣዩ የእስራኤላውያን ትውልድ የእነዚህን ግዙፍ
የእምነት ሰዎች የካሌብና የኢያሱን ምሳሌ መከተሉን ያሳያል። አሮጌው ትውልድ
አገልግሎቱን እየጨረሰ ሲሄድ፣ ተግዳሮቶችን ለመጋፈጥ እና እግዚአብሔር
ለእስራኤል ያለውን እቅድ ለመፈጸም ዝግጁ የሆነ አዲስ ትውልድ አለ።
ካሌብ ኢያሱን “ይህን ኮረብታማ አገር ስጠኝ” ብሎ ከጠየቀው
በተለየ መንገድ በባሏ የተበረታታችው አክሳ አባቷ ያሳየውን እምነትና ውሳኔ
አሳይታለች። በካሌብ ተምሳሌትነት አክሳም ምድሪቱን ለመውረስ የተገባውን
የተስፋ ቃል ፍጻሜ በቆራጥነቷ እና በድፍረትዋ አስቀጥላለች።
በእርግጥም ምድሪቱ ከያህዌ ለእስራኤል የተሰጠች ስጦታ ናት፣ ነገር
ግን እስራኤል የጌታን የተስፋ ቃል በእምነት እና በድፍረት በመናገር መውሰድ
ነበረባቸው። የአክሳ ቆራጥነት በወንጌል ውስጥ የተገለጹትንና ለራሳቸው
እና ለቤተሰባቸው የኢየሱስን በረከት እስኪያገኙ ድረስ ተስፋ ባለመቁረጥ
በሕዝቡም ሆነ በደቀ መዛሙርቱ ግፊት ወደኋላ ያልተመለሱትን ሴቶች ጽናት
አስቀድሞ ይናገራል።
ሉቃስ 18:1-5ን ያንብቡ። በዚህ ጥቅስ ውስጥ ምን ትምህርት እናገኛለን?
የእምነትን ችቦ ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ እግዚአብሔር የሰጠንን ተልዕኮ
ለማሳካት ወሳኝ ነው። በአንድ በኩል እምነትን ለቀጣዩ ትውልድ የማስተላለፍን
ተግዳሮቶች ያስቡ፡ በሌላ በኩል ደግሞ ወጣቶች በእግዚአብሔር ሥራ የበለጠ
ኃላፊነት ሲሰጣቸው ስለሚያገኟቸው እድሎች ያስቡ። ወጣቶች መልካም
መሪዎች እንዲሆኑ ለማመቻቸት እና ለማሰልጠን ምን ማድረግ አለብን? በዚህ
ሂደት ውስጥ የእኛ ተምሳሌት መሆን ምን ያህል ወሳኝ ነው?
ለእስራኤል ነገዶች የተመደቡት ግዛቶች ድንበር ላይ የድንበር ምልክቶች የሆኑት የቦታ ስሞች ረዣዥም ዝርዝሮች ሲጠናቀቁ የሁለቱን ጀግኖች የካሌብን እና የኢያሱን የመሬት ድልድል ዘገባ ይዘዋል። ካሌብ ርስቱን አስቀድሞ ተቀበለ፣ ኢያሱ ግን የመጨረሻውን ተቀበለ። እስከዚህ ነጥብ ድረስ ኢያሱ መሬቱን ለእስራኤል ነገዶች ሲያከፋፍል ቆይቶ፣አሁን ደግሞ የእስራኤል ልጆች ለኢያሱ ርስት የሚሰጡበት ጊዜ ደረሰ። ኢያሱ 19:49-51ን ያንብቡ። ምድሪቱን ያካፈለው ታላቁ የእስራኤል መሪ ርስቱን በመጨረሻ መቀበሉ ምን አንድምታ አለው?
ኢያሱ የተቀበላት ከተማ ተምናሴራ የምትባል ስትሆን በሁለት ቃላት
የተዋቀረ ስም ያላት ናት። የመጀመሪያው ተምና ትርጉሙ መቁጠር ወይም
መመደብ ከሚለው ግሥ (መናህ) የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ክፍል ወይም
ግዛት ማለት ነው። ሁለተኛው ቃል ከዕብራይስጥ ግስ ሴራች የተገኘ ሲሆን
ትርጉሙም ትርፍ ወይም የቀረ ማለት ነው (ከዘጸ. 26፡12 ጋር ያነፃፅሩ)።
የኢያሱ ከተማ ስም የተረፈው ክፍል ወይም የቀረው ግዛት ተብሎ ሊተረጎም
ይችላል።
ኢያሱ ከተረፈው የመረጣት ከተማ ስም የእስራኤል ሁለተኛ መሪ
የነበረውን ክቡር ባህሪ የሚመሰክር ነው። በመጀመሪያ ደረጃ፣ ሁሉም
ሰዎች ድርሻቸውን እስኪያገኙ ድረስ ጠበቀ፤ ከዚያም ኢያሱ ብዙ ሕዝብ
ካላቸው የምድሪቱ ግዛቶች አንዱን ወይም እጅግ አስደናቂ ከሆኑት ከተሞች
አንዱን ርስት አድርጎ አልመረጠም። ነገር ግን ልከኛ የሆነች ከተማን ወይም
ምናልባትም የፈራረሰችዋን ከተማ በአድካሚ ሥራ መልሶ ለመገንባት አስቦ
መረጣት (ከኢያሱ 19፡50 ጋር ያነፃፅሩ)።
ከዚህም በላይ ተምና ሴራህ መቅደሱ አካባቢ ይገኝ በነበረው በሴሎ
አቅራቢያ የምትገኝ ከተማ ነች። ይህ ደግሞ ኢያሱ ቅድሚያ የሚሰጣቸው ነገሮች
የት እንዳሉና ልቡ የታሰረበትን ቦታ ያሳያል። በእርግጥ፣ አዲስ የተወለደው
የእስራኤል ሕዝብ ወደ ተስፋይቱ ምድር ከተመራ በኋላ፣ እና በአምላክ እርዳታ
እያንዳንዱ ነገድ እና ቤተሰብ ርስት ካገኘ በኋላ ኢያሱ የበለጠ አስደናቂ ውርስ
እንዲሰጠው ቢጠይቅ አይቃወሙትም ነበር። ሆኖም ኢያሱ በጣም አስፈላጊ
በሆነው ነገር ላይ በማተኮር ቀለል ያለ ሕይወት በመምራት ረክቷል፤ ስለዚህም
በኋላ በዳዊት የተገለጸውን ጸሎት አመልክቷል፡- “እግዚአብሔርን አንዲት ነገር
ለመንሁት እርስዋንም እሻለሁ፤ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ በእግዚአብሔር ቤት
እኖር ዘንድ፥ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኘውንም አይ ዘንድ፥ መቅደሱንም
እመለከት ዘንድ።” (መዝ. 27:4)።
ከኢያሱ አመለካከት ጋር በተያያዘ ምን ትምህርት እናገኛለን? በህይወታችንስ
ተግባራዊ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?
የታላላቅ የእምነት ጀግኖችን የሕይወት ምሳሌ ማሰላሰል ለመንፈሳዊ እድገታችን አስፈላጊ ነው። በተመሳሳዩ የእኛ ዋናው ምሳሌ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው- ህይወቱ እና ትምህርቱ። በኢየሱስ ሕይወት ላይ ማተኮር የሚለውጠን እንዴት ነው? ዕብ. 12:1-2፣ 2 ቆሮ. 3፡18ን ይመልከቱ።
በሎስ አንጀለስ የካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ የነርቭ ሳይንቲስት የሆኑት
ማርኮ ኢኮቦኒ የነርቭ ሴሎች (mirror neurons) ተግባር ላይ ጥናት
ሰርተዋል። እነዚህ ትናንሽ የሴል ክፍሎች የሚሠሩት አንድን ዓይነት ድርጊት
ስንፈጽም ማለትም እንደ መሳቅ ወይም አንድን ሰው ማቀፍ እንዲሁም ሌላ
ሰው ተመሳሳይ ድርጊት ሲፈጽም ስንመለከት ነው። የእነዚህ ነርቭ ሴሎች
እንቅስቃሴ በማየት እና በመሥራት መካከል ያለውን ልዩነት ያጠበዋል።
ኤለን ጂ ዋይት የኢየሱስን ባህሪ የመመልከትን አስፈላጊነት ስትናገር፡-
“ወደ ኢየሱስ መመልከት ስለ እግዚአብሔር የበለጠ ግልጽና ብሩህ አመለካከት
እንዲኖረን ያደርጋል፡ እርሱን በመመልከትም እንለወጣለን። መልካምነትና
ለሌሎች የምናሳየው ፍቅር የተፈጥሮ ባህሪያችን እየሆነ ይሄዳል። እርሱን
እየመሰልን እናድጋለን፡ ስለ እግዚአብሔር ያለን የእውቀት መጠንም እየሰፋ
ይሄዳል። አብልጠን ከሰማያዊው ዓለም ጋር እየተገናኘን ስንሔድ ዘላለማዊ
የማያቋርጥ ጥበብና የዕውቀት ሃብት እየተቀበልን እንሄዳለን።”-ኤለን የክርስቶስ
ምሳሌያዊ ትምህርቶች፣ ገጽ 197 (በአማርኛው)።
ሮም 12:1-2ን ያንብቡ። በሕይወታችን ውስጥ እርስ በርስ የሚጋጩት የትኞቹ
ሁለት ሂደቶች ናቸው? ለትክክለኛው ቦታ እንደምንሰጥ እንዴት እርግጠኛ
መሆን እንችላለን?
ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ሮሜ ሰዎች በጻፈው መልእክት ማጠቃለያ
ምዕራፍ ላይ ሕይወታችንን ለመቅረጽ ስለሚጥሩ ሁለት ተቃዋሚ ኃይሎች
ተናግሯል። በአንድ በኩል፣ በዙሪያችን ያለው ዓለም፣ በተለያዩ ተፅዕኖዎች፣
በውስጣችን ከውጭ ወደ ውስጥ የሚሠራ መስተጋብር በመፍጠር በየዕለቱ
በራሱ ሊያስገድደን ይሞክራል።
ይህንን ተጽእኖ ለመቋቋም መንፈስ ቅዱስ ከውስጥ ወደ ውጭ
ሊለውጠን የሚችለው አባጨጓሬ ሜታሞርፎስ ወደ ውብ ቢራቢሮነት
ከሚለውጥ መንገድ ጋር በሚመሳሰል መልኩ ነው። ያ ሂደት እንዲካሄድ ግን
እራሳችንን ለእግዚአብሔር ቀድሰን በኛ የጀመረውን መልካም ሥራ እንዲቀጥል
ልንጠይቀው ያስፈልጋል (ፊልጵ. 1፡6))። በመጨረሻ፣ በመንፈስ ለመመላለስ፣
በቅጽበት፣ በንቃተ ህሊና ምርጫ ማድረግ አለብን።
“ካሌብ እሱ ስለ ከነዓን የተናገረው ሰላዮቹ
ከተናገሩት ክፉ ወሬ ጋር በተቃረነ ጊዜ እምነቱ እንደነበረ ሁሉ በዚህም ሰዓት
እንደዛው ነበረ። ሕዝቡን ከነዓንን እንዲወርሱ ለማድረግ እግዚአብሔር የገባውን
ቃል አምኖ እግዚአብሔርን በፍጹም ልቡ ተከተለ። ከህዝቡ ጋር በበረሃ
ተንከራቷል፣ ከጥፋተኞቹ ጋር ሸክሙንና ተስፋ መቁረጡን አብሮ ተጋፍጧል፡
ስለእነዚህ ነገሮች ከማማረር ይልቅ ሌሎች ወንድሞቹ በበረሃ ሲሞቱ ጌታ
ምህረቱን አብዝቶ ስለ ጠበቀው ያመሰግን ነበር። ከነዓን ከገቡ ጀምሮ ብዙ
ትግሎች፣ ማዕበሎች፣ መቅሰፍቶች ቢኖሩም እግዚአብሔር ስለጠበቀው
ሰማንያ ዓመት አልፎት እንኳን ኃይሉ አልደከመም። ለራሱ የጠየቀው የተያዘ
ቦታን ሳይሆን ሰላዮቹ እንኳን ለመውረስ ይከብዳል ብለው ያሰቡትን ቦታ ነበር።
የካሌብን ጥያቄ ያነሳሳው ክብር ወይም ሙገሳ ፍለጋ አልነበረም። የቀድሞው
ጦረኛ ሕዝቡ እግዚአብሔርን የሚያከብሩበትን ተምሳሌት ለመስጠት እና
አባቶቻቸው የማትሽነፍ ብለው የፈሯትን ከተማ በሙላት እንዲወርሱ
ለማበረታታት ይህን አደረገ። የሃይማኖት አባቶችና ነብያት፣ ገጽ 512-513
“ለካሌብ ድፍረትን የሰጠው፣ ሰውን ከመፍራት የጠበቀው እና
በድፍረት እንዲቆም ያስቻለው በእግዚአብሔር ላይ የነበረው እምነት ነበር።
እያንዳንዱ እውነተኛ የመስቀሉ ወታደር የሰማይ ሰራዊት የጦር መሪ በሆነው
ሃይል በመታመን የማይታለፉ የሚመስሉትን መሰናክሎችን እንዲያልፍ
ጥንካሬና ብርታትን ማግኘት ይችላል።” Ellen G. White, The Advent
Review and Sabbath Herald, May 30, 1912
1. የእኩዮች ተጽዕኖ ምን ያህል ኃይል እንዳለውና ሌሎች በማይናገሩበት ጊዜ
ለመናገር ስለሚጠይቀው ድፍረት ይወያዩ። እምነታችንን በተግባር በማዋል
ረገድ የድፍረት ሚና ምንድን ነው? ትክክል ነው ብለን ለምናምንበት ነገር
እየቆምን ክፉ ከመሆን መራቅ የምንችለው እንዴት ነው?
2. ህይወትዎን እና ባህሪዎን የቀረጹ ከቤተ ክርስቲያንዎ ወይም ከማህበረሰብዎ
ያዩዋቸውን አንዳንድ የእምነት ምሳሌዎች በክፍልዎ ውስጥ ያካፍሉ። ከእነዚህ
ሰዎች ባህሪያት የትኞቹን ልንከተላቸው ይገባናል?
3. ሚዲያ በህይወታችን ላይ ስላለው ተጽእኖ እንወያይ። አቅሙን ለበጎ ዓላማ
እየተጠቀምንበት አሉታዊውን ተጽእኖ ማስወገድ የምንችለው እንዴት ነው?
4. ኢያሱን እንደ መሪ ስላሳየው ትህትና እና ወደ መቅደሱ አቅራቢያ ለመኖር
ስላለው ፍላጎት ጊዜ ወስደው ይወያዩ። የእሱ ምሳሌነት የሚናገረን በየትኞቹ
መንገዶች ነው?