የጎልማሶች ሰንበት ትምህርት

የመጸሐፍ ቅዱስ ጥናት መምሪያ

ስለ ሞት፣ ስለ መሞትና ስለ ወደፊቱ ተስፋ


የመጸሐፍ ቅዱስ ጥናት መምሪያ - 3ኛ ሩብ ዓመት 2022

ከህዳር 17-23

10ኛ ትምህርት

Nov 26–Dec 2




የገሀነም እሳቶች



ሰንበት ከሰዓት

ለዚህ ሣምንት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የሚከተሉትን ጥቅሶች ያንብቡ፡ ማር. 9፡42-48፣ ሚል. 4:1፣ ይሁዳ ቁ. 7፣ 1 ጢሞ. 2:5፣ የሐዋ. ሥራ 2:29፣ 34፣ 35፣ 1ኛ ዮሐንስ 5፡3-12።


የሣምንቱ ጥናት መሪ ጥቅስ “ሁሉን ፈትኑ፤ መልካሙን ያዙ” (1ኛ ተሰሎንቄ 5፡21)።

ጣ ሊያናዊ ገጣሚ ዳንቴ አሊግሪ (1265–1321) ከሞት በኋላ ስላለው የነፍስ ጉዞ የሚናገረውን ዘ ዲቫይን ኮሜዲ የተሰኘ ዝነኛ ልብወለድ ፅፏል። በድርሰቱ ውስጥ ነፍስ በምድር ውስጥ ወደሚገኝ እሳት(ገሃነም) ወይም የሰው መንፈስ ራሱን አጽድቶ ወደ ሰማይ ለመግባት ብቁ ወደሚሆንበት መንጽሔ(ፐርጋቶሪ)፣ ወይም ወደ ገነት ወደ እግዚአብሔር እራሱ መገኘት መግባት ነበረበት። ምንም እንኳን ግጥም፣ ልቦለድ ቢሆንም፣ የዳንቴ ቃል በክርስትያናዊ ሥነ-መለኮት ላይ በተለይም የሮማ ካቶሊክ ሥነ-መለኮት ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ አሳድሯል። ከሞተ ሰው የወጣች ነፍስ ወደ ገሀነም፣ ወይም ወደ መንጽሔ፣ ወይም ወደ ገነት ትሄዳለች የሚለው መሠረታዊ አስተሳሰብ ለዚያች ቤተ ክርስቲያን መሠረት ነው።

ብዙ ወግ አጥባቂ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮች ከሞት በኋላ ወደ ገነት የምትወጣ ወይም ወደ ሲኦል የምትወርድ የማትሞት ነፍስ እንዳለች ያምናሉ። በእርግጥም የሰው ነፍስ ካልሞተች አካሉ ከሞተ በኋላ ወደ አንድ ቦታ መሄድ አለባት። በአጭሩ፣ ስለ ሰው ተፈጥሮ ያለው የተሳሳተ ግንዛቤ አስከፊ ሥነመለኮታዊ ስህተቶችን አስከትሏል። በዚህ ሳምንት ከእነዚህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆኑ ንድፈ ሐሳቦች መካከል አንዳንዶቹን እንዲሁም ከሞት በኋላ ስለሚሆነው ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ስለሚናገረው ነገር እንነጋገራለን። *ለህዳር 24 ሰንበት ለመዘጋጀት የዚህን ሳምንት ትምህርት ያጥኑ።

ህዳር 18
Nov 27

የማይሞቱ ትሎች?


ማርቆስ 9:42-48ን ከኢሳይያስ 66:24 ጋር ያነፃፅሩ። “ትላቸው አይሞትም” የሚለውን አገላለጽ እንዴት እንረዳው (ማርቆስ 9:48)?



አንዳንዶች “ትል” የሚለውን ነጠላ ስም (ማር. 9:48) ከአካል የሚወጣውን የክፉዎች ነፍስ ወይም መንፈስ ለማሳየት ነው ብሎ በማመን ከሞት በኋላ ወደ ሲኦል እንደሚበርና ወደማይሞትበትና ዘላለማዊ ሥቃይ እንደሚደርስበት የሚያመለክት እንደሆነ አድርገው ይገልጹታል። ነገር ግን ይህ አተረጓጎም ሞት ምንም የማናውቅበት እንቅልፍ መሆኑን የሚያስተምረውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተሳሰብ አያንጸባርቅም። እንዲሁም የዚህን ክፍል የብሉይ ኪዳን ዳራ ችላ ይላል። እንደ እውነቱ ከሆነ “ነጠላው ‘ትል’ በአጠቃላይ ለ‘ትሎች’ ጥቅም ላይ ይውላል—ይህ ማለት አንድ ነጠላ ትል ማለት አይደለም። እየተናገረ ያለው በሚበሰብስ አካል ላይ የሚመገቡትን ትሎች ነው።”—ሮበርት ጂ. ብራቸር እና ዩጂን ኤ. ኒዳ፣ የኤ ተርጓሚው ሃንድቡክ ኦን ዘ ወንጌል ኦቭ ማርቆስ (ለንደን፡ ዩናይትድ ባይብልስ ሶሳይቲስ፣ 1961)፣ ገጽ. 304.

በማርቆስ 9፡48 ኢየሱስ የጠቀሰው ኢሳይያስ 66፡24ን ማለትም “ወጥተውም በእኔ ያመፁብኝን ሰዎች ሬሳቸውን ያያሉ፤ ትላቸው አይሞትምና፥ እሳታቸውም አይጠፋምና፤ ለሥጋ ለባሽም ሁሉ አስጸያፊ ነገር ይሆናሉ።” የሚለውን ጥቅስ ነው። ይህ አስፈሪ ምሳሌያዊ ትዕይንት የአምላክ ጠላቶች በምድር ላይ የሞቱበትንና የጠፉበትን የጦር ሜዳ ትዕይንት ይገልፃል። በእሳት ያልተበላው አካል በትል ወይም ምናልባት መጀመሪያ በትል ከዚያም በእሳት ይጠፋል። ያም ሆነ ይህ፣ ማንኛውም ነፍስ ከሥጋ ጥፋት አምልጦ ወደ ሲኦል ስለመብረሩ ምንም ዓይነት ማጣቀሻ የለም።

ግን ፈጽሞ የማይሞቱት “ትሎች”ስ? የኢሳይያስ 66፡24 ዘይቤያዊ አነጋገር (በማርቆስ 9፡48 የተጠቀሰው) እነዚህ ትሎች የማይሞቱ መሆናቸውን አያመለክትም። (የማይሞቱ ትሎች?) አጽንዖቱ ትሎቹ አጥፊ ተግባራቸውን ሳይጨርሱ አይቀሩም የሚል ነው። በሌላ አነጋገር ትሎቹ እነዚህ አካላት እስኪጠፉ ድረስ መብላታቸውን ይቀጥላሉ። በአንጻሩ፣ የእግዚአብሔር ታማኝ ልጆች “በአዲሱ ሰማይና አዲስ ምድር” በደስታ ይቀመጣሉ እና እግዚአብሔርን በፊቱ ያመልካሉ (ኢሳ. 66፡22, 23)። ኢየሱስ እነዚህን ተቃራኒ የሆኑ እጣ ፈንታዎች ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ አንድ ሰው በትልና በእሳት የሚጠፋ ሙሉ አካል ከሚኖረው ይልቅ ያለ እጅ፣ እግር ወይም ዓይን እንኳ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ቢገባ እጅግ የተሻለ እንደሚሆን መናገሩ ምንም አያስደንቅም (ማርቆስ 9:42-48)።

በመጨረሻ፣ ሙሉ በሙሉ ድነናል ወይም ሙሉ በሙሉ ጠፍተናል። መካከለኛ ቦታ የለም። የዘላለም ሕይወት ሊኖረን ይችላል ወይም የዘላለም ጥፋት ይገጥመናል። ዛሬ ምን ምርጫዎች ማድረግ ይኖርብን ይሆን? ይህ እውነታ ማለትም የዘላለም ሕይወት ወይም የዘላለም ጥፋት—በምርጫዎቻችን ላይ ምን ተጽዕኖ ያሳድራል?

ህዳር 19
Nov 28

የገሀነም እሳቶች


እንግሊዛዊው የሮም ጳጳስ ጆን ፈርኒስ ለልጆች ባዘጋጀውና “የገሀነም ጨረፍታ” የሚል ርዕስ ባለው ትንሽዬ መጽሐፍ ውስጥ ከሠማይና ከምድር በሚበልጡ ትላልቅ የእሳት ብረት ኳሶች አማካኝነት የሚፈጸም የዘላለም መቃጠል እንደሆነ በምሳሌ ይናገራል። “በየመቶ ሚልዮን አመቱ አንዲት ወፍ ትመጣና ያንን ታላቅ የብረት ኳስ በላባዎቿ ትነካዋለች።” ፀሐፊው የኃጢአን በገሀነም መቃጠል ወፎቹ ከዘመናት በኋላ እየመጡ ሲነኩት የብረት ኳሱ ከሳሳ በኋላም የሚቀጥል ነው ብሎ ሞግቷል።

የሚያሳዝነው ነገር ዛሬም ድረስ ብዙ ፕሮቴስታንቶች፣ ስለ ሚጠፉት ሰዎች ዕጣ ፈንታ ተመሳሳይ ሀሳብ ማመናቸው ነው። ሚልክያስ 4፡1ን እና ይሁዳ ቁጥር 7ን ያንብቡ። እነዚህ ጥቅሶች የዘላለም እሳት ወይም የሚጠፉት ሰዎች በዘላለም እሳት እንደሚቃጠሉ ወይም በማይጠፋ እሳት ስለመቃጠል ኢየሱስ የተናገረውን(ማቴ. 18፡8፣ ማር. 9፡43) እንድናስተውል የሚረዱን እንዴት ነው?



“ዘላለማዊ” የሚለው ቃል(በዕብራይስጡ ኦላም በግሪኩ አዮን፣ አዮንዮስ) በአውዱ ላይ በመመስረት የተለያዩ ትርጉሞች ሊኖሩት ይችላሉ። ለምሳሌ ከእግዚአብሔር ጋር ተገናኝቶ ሲነገር(ዘዳ. 33፡27) የርሱን ዘላለማዊነት ይገልፃል። ከሰዎች ጋር ተገናኝቶ ሲነገር(ዘፀ. 21፡6) ቃሉ በህይወት እስካሉ ድረስ ብቻ ባለው ጊዜ ይወሰናል። ዘላለማዊን ለእሳት ስንጠቀመው እሳቱ የሚቃጠለውን ነገር በልቶ እስኪጨርሰው ድረስ አይጠፋም ማለት ነው። ይህም ማለት ዘላለማዊው እሳት ዘላለማዊ የሚሆነው ኃጠአተኞችን ሙሉ በሙሉ ስለሚያጠፋቸው “ሥርና ቅርንጫፍም ስለማይተውላቸው” ነው(ሚል. 4፡1)።

ለዘላለም ዘላቂ የሆነ ቅጣት የሚለው አስተምህሮ ከባድ ትርጉም ያለው ነው። ኃጢአተኞች ለዘላለም እየተቀጡ የሚኖሩ ከሆነ ስለዚህ ክፋት መቼም አይጠፋም ማለት ነው። ሁሉም ህይወት “በኃጢአተኛው ሞት ደስ ከማይሰኘው አምላክ” (ሕዝ. 33፡11) የተሰጡ ናቸው(ዘዳ. 32፡39፣ መዝ. 36፡9)። ታድያ ክፉዎች እየተሰቃዩ እንዲቀጥሉ ለምን ህይወት መስጠቱን ይቀጥላል? በህይወት መኖራቸውን ቢያስቆም የተሻለ አሳማኝ አይሆንምን? ኃጢአተኞች እንደሥራቸው መጠን የሚከፈላቸው ከሆነ(ዮሐ. ራዕይ 20፡12) ለአጭር ዘመን የሚኖረው የሰው ህይወት ያለማቋረጥ የሚቀጣው ለምንድነው? ስለዘላለማዊ እሳት የሚናገሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች በሙሉ በራዕይ 20 ከተጠቀሰውና ከሺሁ ዓመት በኋላ ከሚመጣው የእሳት ባህር ጋር የተገናኙ ናቸው(13ኛውን ትምህርት ይመልከቱ)። ስለዚህ አሁንም ያለና ሲያቃጥል የኖረ አድርጎ ማስተማር መጽሐፍ ቅዱሳዊ አይደለም።

የገሀነም እሳቶች የማንፈልጋቸው መሆናቸው እንዳለ ሆኖ ይህ እውነት ከዘላለም ቅጣት በተቃራኒ ስለእግዚአብሔር ፍቅር ምን ይናገራሉ?

ህዳር 20
Nov 29

በመንፅሔ ያሉት ቅዱሳን


የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ገሃነም የማይገባቸው ነገር ግን ገና ለገነት ያልተዘጋጁ ሙታን ከኃጢአታቸው በመንጽሔ ውስጥ ነፅተው ከዚያ ወደ ገነት እንደሚሄዱ ታስተምራለች። በመንጽሔ የሚደርስባቸው መከራ የሚወዷቸው ሰዎች በሚጸልዩት ጸሎትና በሚቀጡት ቅጣት ሊቀንስ ይችላል። የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ካተኪዝም ስለ መንጽሔ ሲናገር “በአምላክ ጸጋና የርሱ ወዳጅ ሆነው የሚሞቱ፣ ነገር ግን ፍጽምና በጎደለው መንገድ የነጹ ሁሉ ስለዘላለማዊ መዳናቸው እርግጠኞች ናቸው። ነገር ግን ወደ መንግሥተ ሰማያት ደስታ ለመግባትና አስፈላጊውን ቅድስና ለማግኘት ሲሉ ከሞት በኋላ መንጻትን ያካሂዳሉ።”— Catechism of the Catholic Church, (New York: Doubleday, 1995) p. 291 ይላል። በተጨማሪም የሙታኑ ስቃይ በሚወዱት ዘመዶቻቸው ጸሎት እና ሟቹን ወክለው በሚያደርጓቸው ድርጊቶች ሊቀንስ እንደሚችል ይናገራል። “ቤተ ክርስትያን ሙታንን ወክሎ የሚደረገውን ምጽዋትና የንስሐ ቅጣት ታበረታታለች።”— Catechism of the Catholic Church, p. 291.

መክብብ 9:10፣ ሕዝቅኤል 18:20–22 እና ዕብራውያን 9:27ን ያንብቡ። እነዚህ ምንባቦች የመንጽሔን ጽንሰ ሐሳብ ውድቅ የሚያደርጉት እንዴት ነው?



የመንጽሔው ዶግማ ለዘላለም የሚያቃጥል ገሀነም የሚባለውን አረማዊ ትምህርት እና ለሙታን መጸለይ የሚባለውን አረማዊ አሠራር ያጣመረ ነው። ይህ ዶግማ በመጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮዎች ለሚያምኑ ሰዎች ተቀባይነት የለውም ምክንያቱም (1) ሙታን ምንም ሳያውቁ በመቃብራቸው ስለሚያርፉ (መክ. 9፡10)፤ (2) የአንዱ ኃጢአተኛ ጽድቅ ወደ ሌላ ኃጢአተኛ ሰው ሊተላለፍ ስለማይችል (ሕዝ. 18፡20-22)፤ (3) አማላጃችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ስለሆነ (1 ጢሞ. 2:5)፤ እና (4) ከሞት በኋላ ንስሃ ለመግባት ምንም አይነት ሁለተኛ እድል ሳይኖር የመጨረሻው ፍርድ ስለሚከተል (ዕብ. 9፡27) ነው።

ይበልጥ አሳሳቢ የሆነ አንድምታ ደግሞ፣ የመንጽሔ ፅንሰ ኃሳብ የእግዚአብሔርን ባሕርይ ማዛባቱ ነው። በእርግጥም፣ “ሰይጣን ከወደቀበት ጊዜ አንስቶ የሰራው ሥራ የሰማዩን አባታችንን በተሳሳተ መንገድ እንዲታይ ማድረግ ነው። ነፍስ አትሞትም የሚለውን አስተምህሮ አመጣ። . . . ለዘላለም የሚነድ ገሀነም አስተምህሮ የሰይጣን ምርት ነበር፤ መንጽሔ የርሱ ፈጠራ ነው። እነዚህ ትምህርቶች የአምላክን ባሕርይ ምስል ያበላሻሉ፤ ምክንያቱም እርሱን ጨካኝ፣ ተበቃይ፣ ግትር እና ይቅር የማይል አድርገው ስለሚስሉ ነው።”— Ellen G. White, Manuscript 51 (Dec. 10), 1890 ሙታን የክርስቶስን ዳግም ምፃት እየጠበቁ በእንቅልፍ ናቸው ከሚለው መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ በተቃራኒ ይህ እይታ በመንጽሔ ውስጥ እንዳሉ ይናገራል፣ አንድ ሰው እነሱን ማውጣት እስኪችል ድረስ እዚያ እየተሰቃዩ ነው ብሎ ያስተምራል።

እንደ መንጽሔ ወይም ዘላለማዊ ስቃይ ያሉ ስህተቶች ስለ አስተምህሮ አስፈላጊነት ምን ያስተምሩናል? የምናምነው በማን መሆኑ ብቻ ሳይሆን የምናምነው ፅንሰ-ኃሳብ አስፈላጊ የሆነው ለምንድነው?

ህዳር 21
Nov 30

አካል አልባ ነፍሳት በገነት


ፕሮቴስታንቶች መንጽሔን ባይቀበሉም ብዙዎች የጻድቃን ሙታን ነፍሳት በአምላክ ፊት በገነት ውስጥ እየተዝናኑ እንደሆነ ያምናሉ። አንዳንዶች እነዚያ “ነፍሶች” አካል የሌላቸው መናፍስት ናቸው ብለው ይከራከራሉ። ሌሎች ደግሞ አካል የሌላቸው መናፍስት እንደሆኑ ነገር ግን በክብር መንፈሳዊ አካል ተሸፍነዋል ብለው ያምናሉ። የሕያዋን ሙታን ሁኔታ ምንም ይሁን ምን፣ እነዚህ ንድፈ ሐሳቦች ስለ ሙታን የመጨረሻው ትንሣኤ እና ፍርድ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረተ ትምህርትን ይጥሳሉ። የጻድቃን ነፍሳት በገነት እየተደሰቱ ከሆነ ለምን ትንሣኤና ፍርድ አስፈለገ (ራዕ. 20፡ 12-14)?

የሐዋርያት ሥራ 2:29፣ 34፣ 35ን እና 1 ቆሮንቶስ 15:16–18ን ያንብቡ። እነዚህ ጥቅሶች ሙታንንና ትንሣኤን በመጠባበቅ ላይ ስላሉት ሰዎች ሁኔታ ብርሃን የሚፈነጥቁት እንዴት ነው?



መጽሐፍ ቅዱስ አሁን በሰማይ ያሉት የሰው ልጆች ሁሉ ወይ እንደ ሄኖክ (ዘፍ. 5፡24) እና ኤልያስ (2ኛ ነገ. 2፡9–11) ሕያዋን ሆነው እንደተለወጡ ወይም እንደ ሙሴ ከሙታን እንደተነሱ ያስተምራል (ይሁዳ 9)፤ እንዲሁም ከክርስቶስ ጋር የተነሱትንም ይጨምራል (ማቴ. 27፡51–53)። ቀደም ሲል እንዳየነው “ከመሠዊያው በታች” እንዲበቀል ወደ እግዚአብሔር የሚጮሁት (ራዕ. 6፡9–11) ነፍሳት ፍትህ እንዲያደርግ ጥሪ ስለማድረጋቸው ዘይቤያዊ አገላለፅ ብቻ ነው እንጂ ነፍስ አትሞትም የሚለውን ጽንሰ ሐሳብ አያረጋግጥም። ያለበለዚያ እነዚህ ሰዎች በዘላለማዊ ሽልማታቸው እየተዝናኑ ያሉ አይመስሉም። እንደ እውነቱ ከሆነ፣ መቃብር ሙታን ምንም ሳያውቁ የመጨረሻውን ትንሣኤና የሚታደሱበትን ጊዜ የሚጠባበቁበት የማረፊያ ቦታ ነው። ሙታን፣ አምነው የሞቱ ሙታን እንኳን በመጨረሻው ትንሳኤ ከሥጋቸው ጋር ለመገናኘት በትዕግስት የሚጠባበቁ ሥጋ ያልለበሱ ነፍሳት አይደሉም።

በተጨማሪም፣ ጳውሎስ በ1ኛ ቆሮንቶስ 15፡18 ላይ፣ የሙታን ትንሣኤ ከሌለ “በክርስቶስ ያንቀላፉት ጠፍተዋል” ሲል ስለ ምን እየተናገረ ሊሆን ይችላል? በገነት ደስታ ውስጥ ካሉ እና ከሞቱ በኋላ ምንም ያህል ረጅም ጊዜ ቢቆዩ እንዴት ሊጠፉ ቻሉ? የአዲስ ኪዳን ማዕከላዊ እና ቁልፍ ትምህርት፣ ክርስቶስ በሚመለስበት ጊዜ የሚሆነው የሙታን ትንሳኤ፣ ጻድቃን ሙታን ከሞቱ በኋላ ወዲያው ወደ ዘላለማዊ ሽልማታቸው ይሄዳሉ በሚለው የሐሰት ትምህርት ዋጋ አልባ ሆኗል። ቢሆንም፣ በተለይ በቀብር ሥነ ሥርዓቶች ላይ ሁሌም እንሰማዋለን።

ለሌሎች ሰዎች ሙታን ተኝተዋል የሚለው ሐሳብ በእረፍት ላይ ከመሆናቸው አንጻርና ምንም ህመም ስለማያውቁ በእርግጥም “የምሥራች” እንደሆነ እንዲገነዘቡ ልንረዳቸው የምንችልባቸው መንገዶች የትኞቹ ናቸው?

ህዳር 22
Dec 01

መጽሐፍ ቅዱሳዊው እይታ


1ዮሐንስ 5:3–12ን ያንብቡ። ሐዋርያው ዮሐንስ “የዘላለም ሕይወት”ን በክርስቶስ ላሉት ብቻ የወሰነው ለምንድን ነው?



ነፍስ አትሞትም ከሚለው መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆነ ፅንሰ ሐሳብ በተቃራኒ የሰው ልጅ በሁኔታ ላይ የተመሰረተ አለመሞትን የሚገልጸው መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ በ1 ዮሐንስ 5:11-12 ላይ በግልጽ ተቀምጧል። የዚህን ወሳኝ ክፍል ትርጉም ለመረዳት እግዚአብሔር ብቻ “የማይሞት” (1ጢሞ. 6፡15-16) መሆኑን እና ብቸኛው የሕይወት ምንጭ እርሱ እንደሆነ (መዝ. 36፡9፣ ቆላ. 1፡ 15–17፣ ዕብ. 1፡2) ማስታወስ ይኖርብናል። ኃጢአት በአዳምና በሔዋን ውድቀት (ዘፍጥረት 3) ወደ ዓለም በገባ ጊዜ እነርሱና ዘሮቻቸው ሁሉ (እኛን ጨምሮ) በሥጋ ሞት እርግማን ሥር ወድቀን የዘላለም ሕይወትን ስጦታ አጣን። ነገር ግን አፍቃሪው አምላካችን የሰው ልጆች የዘላለምን ሕይወት እንዲያገኙ የድነት ዕቅድን ተግባራዊ አደረገ፤ ይህም ከመጀመሪያው የእኛ ሊሆን ይገባ የነበረው ሕይወት ነው። ጳውሎስ እንደጻፈው፡- “ዓለም ሳይፈጠር፥ በፊቱ ቅዱሳንና ነውር የሌለን በፍቅር እንሆን ዘንድ በክርስቶስ መረጠን።” (ኤፌ. 1፡4)።

ሐዋርያው ጳውሎስ ኃጢአት “በአንድ ሰው(በአዳም) ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት” እንዲሁ “በአንድ ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል” የሆነው የዘላለም ሕይወት ስጦታ ለሰው ልጆች ሁሉ ቀረበ (ሮሜ. 5፡12-21)። እዚህ ላይ ጳውሎስ ኃጢአትንና ሞትን ወደዚህ ዓለም ያመጣውን አዳምን በማያሻማ ሁኔታ እየጠቀሰ ነው። ከተላለፈውና ኃጢአትንና ሞትን ወደ ዓለማችን ካመጣው ከአዳም ውጪ ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ምንም ዓይነት ትርጉም ሊያገኝ አይችልም። ስለዚህም ሐዋርያው ዮሐንስ አክሎ “እግዚአብሔርም የዘላለምን ሕይወት እንደ ሰጠን ይህም ሕይወት በልጁ እንዳለ ምስክሩ ይህ ነው። ልጁ ያለው ሕይወት አለው፤ የእግዚአብሔር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም።” (1 ዮሐንስ 5፡11-12) ይላል።

አጠቃላይ ሥዕሉ ይበልጥ ግልጽ የሚሆነው ኢየሱስ “ወልድን አይቶ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወትን እንዲያገኝ የአባቴ ፈቃድ ይህ ነው፥ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ።” (ዮሐንስ 6:40) የሚለውንና “ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል” (ዮሐንስ 11፡ 25) ብሎ የተናገረውን ስንመለከት ነው።

ይህ ማለት የዘላለም ሕይወት በክርስቶስ በኩል የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፣ እሱም በአሁኑ ጊዜ የተረጋገጠ ቢሆንም ሙሉ በሙሉ ተጨባጭ የሚሆነው ከጻድቃን የመጨረሻ ትንሣኤ በኋላ ነው። መደምደሚያው በጣም ቀላል ነው፤ የዘላለም ሕይወት በክርስቶስ ላሉት ብቻ የሚሰጥ ከሆነ በእርሱ ውስጥ የሌሉ የዘላለም ሕይወት የላቸውም (1 ዮሐንስ 5፡11-12)። በተቃራኒው ነፍስ አትሞትም የሚለው ጽንሰ ሐሳብ በገነት ውስጥም ሆነ በሲኦል ውስጥ፣ ለሁሉም የሰው ልጆች፣ በክርስቶስ ላልሆኑትም እንኳ የዘላለም ሕይወትን ይሰጣል። ይህ ትምህርት በብዛት የሚስተማር ቢሆንም መጽሐፍ ቅዱሳዊ አይደለም።

ህዳር 23
Dec 02


ተጨማሪ ሀሳብ


ከኤለን ጂ. ኋይት ታላቁ ተጋድሎ ከሚለው መጽሐፍ ውስጥ “የመጀመሪያው ታላቅ ማታለል” እና “ሙታን ሊያናግሩን ይችላሉ?” የሚል ርዕስ ያላቸውን ምዕራፎች ያንብቡ ። “ሙታን የነቃ ነፍስ አላቸው የሚለው ትምህርት ነፍስ በተፈጥሮዋ አትሞትም በሚለው መሰረታዊ ስህተት ላይ የተመሠረተ ነው፤ ይህም ትምህርት ልክ እንደ ዘላለማዊ ስቃይ፣ ከቅዱሳን ጽሑፎች ትምህርት ጋር የሚቃረን፣ ምክንያታዊም ያልሆነ ነው።

በብዙዎች በተያዘው እምነት መሠረት፣ በሰማያት የተዋጁት ቅዱሳን በምድር ላይ ከሚፈጸሙት ነገሮች እና በተለይም ትተውት ከሄዱት ጓደኞቻቸው ሕይወት ጋር የተቆራኙ ናቸው። ነገር ግን ሙታን የሕያዋንን ችግር ማወቃቸው፣ የሚወዷቸው ሰዎች ሲሠሩት የነበረውን ኃጢአት መመልከታቸው እና በሕይወት ውስጥ የሚያጋጥሟቸውን ሀዘኖች፣ ብስጭት እና ጭንቀት ሲታገሡ ማየት እንዴት የደስታ ምንጭ ሊሆንላቸው ይችላል? በምድር ላይ ባሉ ጓደኞቻቸው ላይ እያንዣብቡ ያሉት ሰዎች ምን ያህል የሰማይን ደስታ ሊያጣጥሙ ይችላሉ? ትንፋሹ ከሥጋው እንደወጣ ንስሐ ያልገባ ሰው ነፍስ ወደ ገሃነም እሳት ትገባለች የሚለው እምነት ምንኛ አስቀያሚ ነው! ጓደኞቻቸው ሳይዘጋጁ ወደ መቃብር ወደ ዘላለማዊ ወዮታና ቅጣት ሲያልፉ የሚያዩ ሰዎች ምን ያህል ጥልቅ ጭንቀት ውስጥ ይገቡ ይሆን!”— Ellen G. White, The Great Controversy, p. 545


የመወያያ ጥያቄዎች



1. ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር ስለ ሙታን ሁኔታ እና ስለ ገሀነም ምንነት የተነጋገሩ ሰዎች ምናልባትም የዳኑ ሰዎች ወዲያውኑ ወደ ሰማይ ይሄዳሉ በሚለው ሐሳብ ብቻ ሳይሆን የጠፉትም በገሃነም ዘላለማዊ ስቃይ ውስጥ ናቸው በሚለው እምነታቸው ምን ያህል ጽኑ አቋም እንዳላቸው ተገንዝበዋል። ይህ ለምን የሆነ ይመስላችኋል? የሟች ዘመዶቻቸው “ከጌታ ጋር ናቸው” ብለው ማመን መፈለጋቸው አንድ ልንረዳው የምንችለው ነገር ነው፤ (ምንም እንኳን ቀደም ብለን እንደተመለከትነው፣ የሞቱት እዚህ ምድር ላይ የነገሮችን ውጥንቅጥ ሲመለከቱ ምን ያህል እንደሚያበሳጫቸው በጥያቄ ውስጥ መሆኑ እንዳለ ሆኖ)። ግን የጠፉ ሰዎች በገሃነም ውስጥ ለዘላለም ይሰቃያሉ ከሚለው አሰቃቂ ኃሳብ ጋር ጠንካራ ትስስር ያለው ለምን ይሆን? ከአባቶች ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ወግ ምን ያህል ኃይለኛ እንደሆነ ይህ እውነታ ምን ያስተምረናል? በሰንበት ትምህርት ክፍልዎ ውስጥ ይወያዩበት።

2. አብዛኞቹ የክርስቲያን ቤተ እምነቶች ነፍስ አትሞትም የሚለውን ኢ-መጽሐፍ ቅዱሳዊ ንድፈ ሐሳብ ከሁሉም ተዛማጅ አስተምህሮዎች ጋር እያወጁ ነው። እንደ ቤተ ክርስቲያን (አሁን ከምንሠራው በተጨማሪ) ስለ ሞትና ስለ ሕይወት ያለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ አመለካከት ለዓለም ለማወጅ ሌላ ምን ማድረግ ይኖርብን ይሆን?

3. የዳንቴ ግጥም ተራ ልቦለድ ቢሆንም፣ ከሞት በኋላ “ነፍስ” ላይ ስለሚሆነው ነገር የሚገልፁ የሐሰት ትምህርቶች በሰዎች አእምሮ ውስጥ እንዲያያዙ በመርዳት ረገድ ከፍተኛ ተጽዕኖ አሳድሯል። የክርስቲያን አስተምህሮ በውጪ ትምህርቶች እንዴት በቀላሉ ተፅዕኖ ውስጥ እንደሚወድቅ ይህ ሁኔታ ምን ትምህርት ይሰጠናል? ዛሬም ቢሆን በክርስቲያናዊ አስተሳሰብ ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ ሌሎች ምን አይነት ክርስቲያናዊ ያልሆኑ ኃሳቦች አሉ? ራሳችንንስ ከእነዚህ ኃሳቦች መጠበቅ የምንችለው እንዴት ነው?




Shalom Teleconference Ministries Inc -- Translated by Ethiopian SDA union SSL